የሲዳማ ፖለቲካ እና የሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች እጣ ፋንታ በሚል ርዕስ በመኮንን የሱፍ ፅፎ ለንባብ ባበቃው ዓምዱ ላይ የተስተዋሉ ግድፈቶቸን አስመልክቶ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ባህል ቱሪዝምና የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ እንዲሁም የሲዳማ ዞን ባህል ቱሪዝምና የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊዎች መግለጫ ሰጥተዋል
የሲዳማ
ፖለቲካ እና የሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች እጣ ፋንታ
በሚል ርዕስ በመኮንን የሱፍ ፅፎ ለንባብ
ባበቃው ዓምዱ ላይ የተስተዋሉ ግድፈቶቸን
አስመልክቶ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ባህል
ቱሪዝምና የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች
መምሪያ እንዲሁም የሲዳማ ዞን ባህል ቱሪዝምና
የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊዎች
መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በዚህ ዕትም ፀሀፊው ያሰፈራቸው በርካታ ሀሳቦች ከእውነታ የራቁና ተጨባጭነት የሌላቸው እንዲሁም የሲዳማ ብሔር ማንነትና ያሉትን ወርቃማ እሴቶቹን በጠራራ ፀሐይ የካደ በጭፍን ጥላቻ የተሞላ የፀሐፊው የሞያ ስነ-ምግባር ግድፈት ጭምር የተስተዋለበት ነው፡፡ ምንም እንኳን ፀሀፊው በፅሁፉ የራሱን የተሳሳተ አስተሳሰብ ለማስረጽ ጥቂት እውነት የሚመስሉ ሀሳቦችን በፅፉ ያካተተ ቢሆንም የፅሁፉ መሰረታዊ ይዘት እና ዝርዝር ጉዳዮች ሲታዩ መሰረት የሌላቸውና የአፍራሽ ሀይሎች ቅጥረኛ የተውሶ ፖለቲካ አራማጅ መሆኑን የሚያመላክት ነው፡፡
በፅሁፉ ከተካተቱት መሰረታዊ ሃሳቦች መካከል1.ኛ. የሲዳማ ብሔር ክልል የመሆን ጥያቄ ስልጣን ያልተቆናጠጡ ልሂቃን ጥያቄ ብቻ ተደርጎ በፅሁፉ የሰፈረው ፍፁም ስህተት መሆኑን ፀሀፊው ሊገነዘብ ይገባል፡፡
የሲዳማ
ህዝብ ክልል የመሆን ጥያቄ እንደማንኛውም
የሀገራችን ጭቁን ህዝቦች በተለያዩ ስርዓቶች
ጭቆናና አፈና ሲፈራረቁበት በመኖሩ ባህሉን፣
ወጉንና ቋንቋውን እንዲሁም ማህበራዊ፣
ኢኮኖሚያዊ ፖለቲካዊ ተጠቃሚነቱን ለማስከበር
ካደረጋቸው ትግሎች መካከል አንዱ ተደርጎ
የሚታይ ነው፡፡
የሲዳማ ህዝብ ክልል የመሆን ጥያቄ ራስን በራስ ለማስተዳደርና የራሱን ማንነት ለማስከበር ጥያቄዎቹን ከዓፄዎቹ ዘመን ጀምሮ በብሔሩ ተወላጆች ለዘመናት በተደራጀና ባልተደራጀ መልኩ ትግል ሲያካሂድ ቆይቷል፡፡ ለምሳሌ የአፄ ሚኒሊክን ጦር በከፍተኛ ደረጃ ተዋግቷል፣ የተደራጀ ትጥቅ የነበረውን አፋኙና ጨቋኙን የደርግ ሰርዓት ለመገርሰስ ከሀገር አልፎ እሰከ ሶማሊያ የዘለቀ እልህ አስጨራሽ የትጥቅ ትግል አድርጓል፡፡
ላለፉት 27 ዓመታትም የሲዳማ ህዝብ በክልል የመደራጀት ጥያቄውን ባገኘው አጋጣሚ በአግባቡ ከመጠየቁም በላይ በ1997 ዓ.ም እንዲሁ በ2010 ዓ.ም በዞኑ ምክር ቤት በሙሉ ድምፅ ውሳኔ አጊኝቶ ለቀጣይ ህዝበ ውሳኔ ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል፡፡
ከዚህ አንፃር የፀሀፊው አገላለፅ ክልል የመሆን ጥያቄን የብሔሩ ተወላጅ ጥቂት ስልጣን ያላገኙ ልሂቃን ተደርጎ የተወሰደው የፅሁፉን ከእውነት የራቀ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡
በክልሉ ያሉት የብሔሩ ተወላጅ የሆኑ የደኢህዴን አመራርም ቢሆኑ በድርጅቱ የተሰጣቸውን ተግባርና ኃላፊነት ህገ-መንግስትን መሰረት ባደረገ መልኩ የሚያስፈፅሙ እና የትኛውም ብሔር ህገ-መንግስታዊ መብቱ እንዲከበር የሚሰሩ እንጂ በደም ትስስር ክልል የመሆን ጥያቄውን ውስጥ ለውስጥ የሚያቀነቅኑ አለመሆኑንም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
2.ኛ. የሲዳማ ህዝብ ክልል የመሆን ጥያቄ በቀድሞውም ይሁን በአሁኑ የሀገሪቱ መሪዎች ተቀባይነት የሌለው ተደርጎ የተቀመጠውም ሀሳብ ፍፁም ስህተት ነው፡፡
ለዚህ ማሳያ ሊሆን የሚችለው የሲዳማ ህዝብ ክልል የመሆን ህገ-መንግስታዊ ጥያቄው ኢህአዴግ በሚመራው ፌደራላዊ ስርዓቱ ውስጥ ተግባራዊ እየተደረገ ባለው አሰራር ማዕቀፍ ውስጥ የሚታይ እንጂ በመሪዎች መልካም ፍቃድ ላይ የተመሰረተ አለመሆኑ ልብ ሊባል ይገባል፡፡ ከዚህም አኳያ ጥያቄው በህገ-መንግስቱ የተቀመጠውን አሰራር በተከተለ መልኩ ምላሽ የሚያገኝ እንጂ እንደፀሀፊው እምነት መሪዎች ሲፈልጉ የሚሰጡት ሲፈልጉ የሚከለክሉት እንዳለሆነ ሊታወቅ ይገባል፡፡
3.ኛ. ፅሁፉ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄን አስመልክቶ በሀዋሳ ከተማ በመገኘት ከብሔሩ ተወላጆች ጋር ባደረጉት ውይትት የሰጡትን ምላሽ አዛብቶ አቅርቦታል፡፡
ይህም በወቅቱ የነበረው የሲዳማ ህዝብ ቁጥር 7ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ መሆኑን እና ክልል እንኳን ብትሆኑ ይርጋለምን ወይም አለታወንዶን የክልሉ ዋና ከተማ ካላደረጋችሁ በቀር ሀዋሳን ዋና ከተማ ማድረግ እንደማይቻል ያስቀመጠው ይገኝበታል፡፡ ይህ የሚያሳየውም የሲዳማ ህዝብንና የሀዋሳ ከተማን ታሪካዊ ትስስር ካለመረዳት በመነጨ እና በግለሰቦች ፍላጎት ላይ የተመሰረተ ፅሁፍ መሆኑን አመላካች ነው፡፡
ሌላው የሀወሳ ከተማ በ1952 ዓ.ም እንደ ከተማ ከመቆርቆሯ በፊት ጀምሮ የሲዳማ አርሶ/አርብቶ አደር ህዝብ አዳሬ በሚል መጠሪያ ለእርሻ እና ለግጦሽ ሲጠቀሙበት ከነበረው በንጉሱ ውሳኔ መሰረት ከተማ ትሁን ሲባልም ሆነ የከተማነት ቅርፅ ስትይዝ በባለቤትነት የቆረቆራት ይህ የሲዳማ ብሔር እንደሆነ የካደ ነው፡፡ ለዚህ ሌላው ማሳያ ከተማዋ ስትቆረቆር በከተማው የሚገኙ መንገዶች፣መንደሮች እና ሰፈሮች ጭምር በብሔሩ ቋንቋ ስያሜ የተሰጣቸው መሆኑም ተጠቃሽ ነው፡፡ በደርግ ስርዓት ወቅትም ቢሆን ከተማዋ በሲዳሞ ክፍለ ሀገር፣ በሲዳማ አውራጃ በሀዋሳ ወረዳ በሚል እንደወረዳ እንደሌሎቹ የሲዳማ ወረዳዎች የሚትታይ እንጂ እንደፅሁፉ የብሔሩ ተወላጅ ቁጥር ከሌሎች ብሄረሰቦች ጋር ለንፅፅር የሚቀርብ እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል፡፡
በዚህ ስርዓትም ቢሆን የህዝብ ቁጥሩ በከተማ ካለው 400000(አራት መቶ ሺህ) ህዝብ ሌላውን በከተማ ውስጥ እየኖረ ያለውን የብሔሩ ተወላጅ ሳያካትት ከ200000(ሁለት መቶ ሺህ) በላይ የሚይዘውን የሀዋሳ ከተማ የገጠሩን ክፍለከተማ ሀዌላ ቱላን ብቻ ማየት በቂ ነው፡፡
4ኛ. በየዓመቱ በሚካሄደው የፊቼ ጨምበላላ በዓል የከተማው ነዋሪ ተሸብሮ በፀሎት እንደሚያሳልፍ፤ ንግድ ቤቶችም ቢሆኑ እንደሚዘጉ ተደርገው የተወሰደው እንዲሁም ያልተዘጉትም ለዘረፋ የተጋለጡ ተደርገው በፅሁፉ የቀረበው ሀሳብም እንዲሁ ከእውነት የራቀ ነው፡፡ ለዚህ ማሳያው በየዓመቱ የሚከበረው የሲዳማ ብሔር የዘመን መለወጫ ፊቼ ጫምበላላ በዓል ለሰፊው የሲዳማ ህዝብ የማንነቱ መገለጫ፣ ከስልጣኔዎች በፊት ጀምሮ የዲሞክራሲ ስርዓት ማሳያ እንዲሁም የሰላም፣ የአንድነትና የመቻቻል ተምሳሌት መሆኑን የሳተ መሆኑ ነው፡፡
ከዚህ ባሻገር በዓሉ በሀዋሳ ከተማ በሚገኘው ትልቁ ጉዱማሌ (በዓሉ በሚከበርበት ስፍራ) ከሌሎች ወንድም ብሔሮችና ብሔረሰቦች ጋር የሚከበር በዓል መሆኑንም የካደ ነው፡፡ በዓሉ ከብሔሩ ተወላጆች አልፎ የሀገር ሀብት ሆኖ በዩኔስኮ በማይዳሰስ ቅርስነት ተመዝግቦ መገኘቱንም ከግምት ውስጥ ያላስገባ ነው፡፡ ለዚህ ማሳያው በዓሉ ከመከበሩ ከአንድ ሳምንት አስቀድሞ የከተማዋ ነዋሪ የሆነው ሌላው ብሔረሰብ ጭምር የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት በመለዋወጥ የተለያዩ ዝግጅቶችን በማድረግ በጉጉት የሚጠብቁት ከመሆኑ ባሻገር በከተማዋ እንደሚከበሩት እንደ ሌሎች ሀይማኖታዊ ክብረ-በዓላት ለከተማው የቱሪዝም ኢንዱስተሪ ትልቅ ግብዓት በመሆን መነቃቃትን የሚፈጠር ነው፡፡ የፊቼ በዓል በሚከበርበት ቀን የተጣላ የሚታረቅበት፣ ያለው ለሌለው አካፍሎ በጋራ የሚበሉበት እንጂ የግጭት ምክንያት የሚሆንበት እሴት የሌለው በዓል መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡
5.ኛ. በፅፉ በዚህ ባሳለፍነው 2010 ዓ.ም በሀዋሳ ከተማ የተከሰተውን ግጭት ከበዓሉ ጋር ለማስተሳሰር የተሞከረውም ፍፁም ስህተት መሆኑ ነው፡፡
በዓሉ እንደሌሎቹ ዓመታት ሁሉ እሴቱን በጠበቀ መልኩ እንዲከበር በቂ ዝግጅት ተደርጎበት ተከብሮ መጠናቀቁን ፅሁፉ የካደ ነው፡፡ በዓሉ ያለምንም የፀጥታ ችግር በሰላም ተከብሮ እንዲጠናቀቀ ከክልሉ መንግስት፣ ከሲዳማ ዞንና ከከተማ አስተዳደሩ የተውጣጣ ግብረ-ሀይል ተቋቁሞ በዚህላይ ዝርዝር ዕቅድ ወጥቶ በተሰራው ስራ በጉዱማሌ በደማቅ የቄጣላ ስነ-ስርዓት ተከብሮ በኢትዮጵያ ህዝብ ብሔራዊ መዝሙር መጠናቀቁንም ፅሁፉ የካደ ነው፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በዓሉ ከተከበረ ከጥቂት ቀናት በኋላ ወቅቱ በሀገራችን በሚገኙ በአንዳንድ አካባቢዎች በሀገር ደረጃ የተጀመረውን ለውጥ የማደናቀፍ እንቅስቃሴዎች እዚህም እዚያም የተስተዋሉበት መሆኑ የማይካድ ሀቅ ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ ከተማችንን በሚመለከት በወቅቱ ከየትኛውም ብሔር ጋር ግንኙነት የሌለው ግጭት የተፈጠረ ሲሆን በግጭቱም በሔር ሳይለይ ግጭቱ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ሲዳማን ጨምሮ በየትኛው በሔር ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡
ፅሁፉ የህንን ግጭት ከብሔር ጋር ለማስተሳሰር የሞከረበት አግባብ ሊታረም የሚገባው ነው፡፡ የሲዳማ ህዝብ ወንድሙ ከሆነው ከወላይታ ህዝብ ጋርም ዘመናትን ያስቆጠረ እስከ ጋብቻ የዘለቀ ወዳጅነትና ትስስር ያለው መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ፀሀፊው ለፃፈው ፅሁፍ ማድመቂያ አድርጎ ለመጠቀምና አፍራሽና የተሳሳተ መረጃ በመልቀቅ ገበያ አገኝበታለሁ ብሎ አስቦ ከሆነ ብሔርን ከብሔር በማጋጨት ትርፍ ማግኘኘት እንደማይቻል በመገንዘብ ከእኩይ ተግባሩ እንዲቆጠብ እንላለን፡፡
የሲዳማ ህዝብ በሀይለማሪያም አመራርነት ወቅት በሲዳማ ንፁሀን ወጣቶች ህይወት ላይ በሎቄ አካባቢ የደረሰውን ጭፍጨፋ በአቶ ሀይለማሪም አመራር ሰጪነት የተፈፀመ በመሆኑ የሲዳማ ህዝብ ቂም በመያዙ የደረሰ ጉዳት ነው ተብሎ የተዘገበውም ፍፁም ስህተት በመሆኑ ሊታረም የሚገባው ነው፡፡
ለዚህ ማሳያው ጭቁኑ የሲዳማ ህዘብ በማንነቱ እንዳይኮራ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነቱ እንዳይረጋገጥ በተለያዩ ጊዜያት የሚደርሱበትን ጭቆና እጁን አጣጥፎ አሜን ብሎ የማይቀበል ህዝብ በመሆኑ በየጊዜው ሰላማዊ በሆነ መልኩ ግን የራሱን ማንነት በህገ-መንግስታዊ ማዕቀፉ ለማስከበር በተለያየ ጊዜያት ሲጠይቅ ቆይቷል፡፡
ከዚህ ጋር ተያይዞ ብዙ ጭፍጨፋና አፈና እንዲሁም አስራት ሲደርስበት የቆየ ህዝብ ነው፡፡ ስለሆነም ግልሰቦች የራሳቸው ሚና አይኖራቸውም ባይባልም የ1995ቱ የሎቄ ጭፍጨፋም የዚሁ አንዱ አካል ተደርጎ የሚወሰድ ሆኖ በዚህ በልማታዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ሽፋን ክራይ ሰብሳቢው ሀይል የፈፀመው ድርጊት እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል፡፡
6.ኛ. ለሀዋሳ ከተማ እድገት የገቢ ምንጭ ፌደራል መንግስትና የክልልል መንግስት ተደረገው በፅሁፉ መጠቀሳቸውም ከእውነት የራቀ በመሆኑ ሊታረም የሚገባው ነው፡፡
ይህ ማለት ከተማዋ ከ90% በላይ ከራሷ ገቢ በመሰብሰብ ለመሰረተ ልማት በማዋል የራሷን ወጪ የምትሸፍን እንጂ በፅሁፉ እንደሰፈረው በክልልና በፌደራል መንግስት ድጋፍ እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል፡፡
በሌላ በኩል ፀሐፊው እንደሚገልፀው ከተማውን አንድ ብሔር ስለመራው ሌሎች ብሔሮች ስጋት ውስጥ ገብተዋል በሚልው መልክ ሳይሆን ከተማውን የሚመሩ አመራር አከላት ኃላፊነታቸውን ከተጠያቂነት ጋር መወጣት በመቻላቸው ከሁሉም በላይ ሰፊውን የከተማውን ህብረተሰብ ባሳተፈ መልኩ ለልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች ቅድሚያ ሰጥተው በመስራታቸው የመጣ ውጤት መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
በመጨረሻም ከላይ ከተጠቀሱት በተጨማሪ እስካሁን ድረስ በከተማ አስተዳደሩ ውስጥ ለተመዘገቡ ስኬቶችና ለታዩ ጉድለቶች በሚዲያ የተደገፈ ፈጣን የህዝብ ግንኙነት ስራ እየተሰራ መቆየቱ ማንም ሚገነዘበው ሀቅ ሆኖ ሳለ ፀሀፊው እውነታውን በመካድ ለተጨማሪ ግጭት ሊዳርግ በሚችል መልኩ ስሜት ቀስቃሽ የሆነ የተዛባ መረጃ ከማስተላለፍ ሊቆጠብ ይገባል፡፡
በዚህ ፅሁፍ የተስተዋለውን መሰረተ ቢስ ውንጀላ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን በአዋጅ ቁጥር 533/1999 በን.አ42 መሰረት ይህ መፅሔት ከገበያ ተለቅሞ እንዲወጣና አሳታሚ ድርጅቱ የእርምት ማስተካከያ እንዲሰራ በመጠየቅ ይህ ካሆነ የሲዳማ ዞን አስተዳደር እና የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ጉዳዩን በህግ አግባብ ለመጠየቅ የሚገደድ መሆኑን ጭምር እንገልፃለን፡፡
ግልባጭ፡-
ለኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን
አዲስ አበባ
ለደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳደር ፅ/ቤት
ለደቡብ ክልል የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት
ለሲዳማ ዞን አስተዳደር
ለሀዋሳ ከተማ አስተዳደር
ለሲዳማ ዞን አስተዳደር ባህል ቱሪዝምና የመንግስት ኮሙኒኬሽን መምሪያ
ለሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ባህል ቱሪዝምና የመንግስት ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን መምሪያ
ሀዋሳ
Comments
Post a Comment