በወንዶ ገነት አካባቢ በሚገኘው በተፈጥሮ ደን ላይ ተነስቶ የነበረው የሰደድ እሳት ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ስር መዋሉ ተገለፀ፡፡
በሲዳማ ዞን የወንዶ ገነት ወረዳ የመንግስት ኮሚኒኬሽን የጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ዮሐንስ ጉራቻ እንደገለፁት መጋቢት 8 ቀን 2ዐዐ4 ዓ/ም ከቀኑ 6 ሰዓት ጀምሮ ባልታወቀ ምክንያት ተነስቶ የነበረው ሰደድ እሳት ለ2 ተከታታይ ቀናት በመቆየቱ በ2ዐዐ ሄክታር መሬት ላይ የነበረ የተፈጥሮ ደን ሊወድም ችሏል፡፡
በተነሳው የሰደድ እሳት ምክንያት በርካታ ብርቅዬ አዕዋፋትና የዱር እንስሳት ከቦታው መሰደዳቸውን የገለፁት ምክትል ኃላፊው የእሳቱን መንስኤ ለማጣራት የወንዶ ገነት ደን ኮሌጅ ጉደዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ጥናት እያካሄደ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የእሳቱን ኃይል በቁጥጥር ስር ለማዋል የፌዴራል ፣ የዞንና የወረዳው ፖሊስ እንዲሁም የኮሌጁ ሠራተኞችና የአካባቢው ህብረተሰብ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማድረሃጋቸውንም ገልፀዋል፡፡
የወንዶ ገነት ደን ኮሌጅ ማነጂንግ ዳይሬክተር አቶ ወንድሙ አክሊሉ በአካባቢው በየዓመቱ ለግል ጥቅማቸው ሲሉ በደኑ ላይ የሰደድ እሳት የሚለቁ ግለሰቦች እንደሚስተዋሉ አውስተው ይህ ተግባር ህዝብንና መንግስትን የሚጐዳ በመሆኑ ከድርጊታቸው ሊቆጠቡና ደኑን በባለቤትነት ሊጠብቁ እንደሚገባቸው ገልፀዋል ሲል ሪፖርተራችን ካጀ ጀንቦላ ከበንሳ ቅርንጫፍ ጣቢያችን ዘግቧል፡፡
Comments
Post a Comment